የኢትዮጵያን የታዳሽ ኀይል ሀብት ወደ ዶላር የሚቀይረው የቢትኮይን አሠሣ
newsare.net
በየካቲት ወር 2016 ዓ.ም. ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፉን የክሪፕቶ ከረንሲ መገበያያ ዓይነቶች መካከል አንዱ የኾነውን የቢትኮይን ማይኒንግ ወይም በግርድፍ ትርጉሙ በይየኢትዮጵያን የታዳሽ ኀይል ሀብት ወደ ዶላር የሚቀይረው የቢትኮይን አሠሣ
በየካቲት ወር 2016 ዓ.ም. ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፉን የክሪፕቶ ከረንሲ መገበያያ ዓይነቶች መካከል አንዱ የኾነውን የቢትኮይን ማይኒንግ ወይም በግርድፍ ትርጉሙ በይነ መረብ አሠሣ (ፍለጋ) በመጀመር ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር ኾነች።አገሪቱ፣ ባለፉት 15 ዓመታት በገነባቻቸው የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ኀይል ማመንጫ ግድቦች አማካይነት ከፍተኛ የኀይል አቅርቦት ቢኖራትም፤ የኤሌክትሪክ ኀይሉን ለተጠቃሚው ሕዝብ እና ለሚፈለገው ግልጋሎት ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ዐቅም አለመገንባቷን ባለሞያዎች ይናገራሉ። ይህን ክፍተት በመጠቀም፣ ከ22 በላይ የሚደርሱ ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ተቋማት፣ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኀይል አቅርቦት የሚሻውን የቢትኮይን ማይኒንግ ወይም በይነ መረባዊ አሠሣ ሥራ ጀምረዋል። ከዚኽም ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት ከዘርፉ 55 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝታለች። የያዝነው የ2017 ዓ.ም ሲጠናቀቅ ደግሞ፣ 123 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደምታገኝ፣ የዓለም አቀፍ የገበያ ትንተና ገጽ የኾነው Nasdaq ትንበያ ይጠቁማል። በኢትዮጵያ፣ በክሪፕቶ ከረንሲ ዓይነቶች ለመገበያየት፣ አኹንም ድረስ የሕግ ማሕቀፍ ስላልተበጀለት ክልክል ቢኾንም፣ ቢትኮይንን ፈልጎ የማግኘት ሥራ ላይ መሰማራት ለሚፈልጉ ፈቃድ መስጠት ተጀምሯል። ይኹን እንጂ፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አገልግሎት በዘርፉ የተሰማሩ ተቋማትን የኀይል ፍላጎት በተፈላጊው መጠን ሟሟላት ስለመቻሉ ጥርጣሬዎች ይነሣሉ። በጎርጎርሳውያኑ የዘመን አቆጣጠር በ2008፣ ሳቶቺ ናካሞቶ በሚል የብዕር ስም በሚታወቅ የቴክኖሎጂ ባለሞያ የተፈለሰፈው ቢት ኮይን፣ ሰዎች በማናቸውም ሰዓት፣ በየትኛውም የዓለም ክፍል፣ ያለባንክ እና ያለምንም የገንዘብ መተመኛ ለመገበያየት የሚያስችል ሲኾን፣ በበይነ መረብ ላይ ባለቤቱ በሚመሠርተው የምስጢር ቁልፍ ብቻ የሚንቀሳቀስ ነው። መሥራቹ ሳታቺ ናካሞቶ፣ በቁጥር የተወሰኑ ቢትኮይኖችን፣ ኮድ ባላቸው ቁልፎች በመቆለፍ ሰዎች አሥሠው በማግኘት እንዲጠቀሙባቸው ለቋል። በኢትዮጵያ ፈቃድ አውጥተው የቢትኮይን ማይኒንግ ወይም ፍለጋ ከጀመሩ ተቋማት መካከል ቀዳሚ የሆነው፣ QRB ላብስ ተቋም መሥራች ነሞ ሥምረት፣ አገሪቱ የምታመርተውን የኤሌክትሪክ ኀይል አቅርቦት ተደራሽ የሚያደርግ መሠረተ ልማት አለመኖሩን ጠቅሶ፣ በቢትኮይን አሠሣ፥ በግድቦቹ የሚባክነውን የኤሌክትሪክ ኀይል አገሪቱ ወደ ዶላር እንድትለውጥ ያግዛል፤ ይላል። በአኹን ሰዓት አንድ ቢትኮይን፣ በዓለም ገበያ ላይ እስከ 90ሺሕ የዩናይትድ ስቴትስ ዶላር ይተመናል። ይኹን እንጂ፣ አንድን ቢትኮይን አሥሦ ለማግኘት 155 ሺሕ ኪሎዋት የሚኾን የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ያስፈልጋል። ይህ አኀዝ በኢትዮጵያ 1ሺሕ33 መኖሪያ ቤቶችን ለማብራት ያስችላል። እ.ኤ.አ በ2023፣ 50ሺሕ 294 ኪሎ ቶን የኤሌክትሪክ ኀይል መጠቀሟን፣ ኢንተር ዳታ የተሰኘ ተቋም ድረ ገጽ አመላክቷል። በዩናይትድ ስቴትስ ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ማዕከል በኾነው ሲልከን ቫሊ ባለሞያ የኾነው ቃል ካሳ፣ በኢትዮጵያ ክርፕቶ ከረንሲ እና የቢትኮይን አሠሣ ምን እንደ ኾኑ፣ ወጣቶች እና ፖሊስ አውጭዎች ግንዛቤ እንዲኖራቸው ይሠራል። ለብዙዎች በቀላሉ ለመረዳት የሚያዳግተውን ፅንሰ ሐሳብ ለአሜሪካ ድምፅ አብራርቷል። ኢታን ቬራ፣ መቀመጫውን በሲያትል ዋሺንግተን ያደረገውና ኢትዮጵያን ጨምሮ በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች፣ ለቢት ኮይን አምራች ተቋማት የሶፍትዌር እና የማሽን አቅርቦትን የሚያመቻቸው የሉግዘር ቴክ ባልደረባ ነው፤ በኢትዮጵያ ከሚገኙ አሣሽ ድርጅቶችም ጋራ አብሮ ይሠራል። ኢትዮጵያ በታዳሽ ኀይል ማመንጨት ኀይሏ ተመራጭ ኾናለች፤ ይላል። ኢታን ቬራ፣ ቢትኮይን፥ የአገሪቱን ሕዝብ የኀይል አቅርቦት እየተሻማ ይኾን እንደኾን፣ በአሜሪካ ድምፅ ለቀረበለት ጥያቄ፤ በኢትዮጵያ የሚመነጨው ኀይል በተገቢው መንገድ ለማኅበረሰቡ ተደራሽ አለመኾኑን ጠቅሶ፣ በቢትኮይን ፍለጋ ላይ የተሰማሩ ተቋማት የኀይል መጠኑ ሳይባክን አገሪቱ ገቢ እንድታገኝ በማስቻል እያገዙ ነው፤ ይላል። አብዛኛዎቹ በቢት ኮይን አሠሣ እና ዝላይ የተሰማሩ ተቋማት፣ ድርጅቶቻቸውንና ማሽኖቻቸውን በኀይል አመንጪ ግድቦች አቅራቢያ እንደሚተክሉ ኢታን ቬራ ይናገራል። በአንድ እና በሁለት ሰው የሚሠራውና እምብዛም የሥራ ዕድል ፈጠራ ዐቅም የሌለው የቢት ኮይን አሠሣ ሥራ፣ አገሪቱ ተጨማሪ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ በማድረግ ስኬታማ ኾኗል። አገሪቱ፣ ባለፈው ዓመት ብቻ 55 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ስታደርግ፤ የያዝነው የ2017 ዓ.ም ሲጠናቀቅ 123 ሚሊየን ዶላር ገቢ እንደምታገኝ፣ የዓለም አቀፍ የገበያ ትንተና ገጽ የኾነው Nasdaq ተንብይዋል። ይኹን እንጂ፣ ማሽኖችን በማስገባት እና ከተቋማት ጋራ ሥራን በማሳለጥ፣ ተግዳሮቶች እና መጓተቶች እንደነበሩ፣ የQRB ላብስ መሥራች ነሞ ሥምረት ተናግሯል። የለግዘር-ቴክ ሥራ አስፈጻሚ ኢታን ቬራም፣ አገሪቱ ሥራውን ለማሳለጥ የሚረዳ የፌደራል እና የክልል ፖሊሲዎች ማዘጋጀት እንደሚያስፈልጋት ጠቁሟል። በሌላ በኩል፣ በኢትዮጵያ ፈቃድ አውጥቶ ቢትኮይን መፈለግ የሚቻል ሲኾን፣ ቢትኮይንን ጨምሮ በሌሎች የክሪፕቶ ከረንሲ ዓይነቶች መገበያየት ግን ሕገ ወጥ እንደኾነ፣ የገንዘብ ሚኒስቴር በኅዳር ወር 2017 ዓ.ም. ባረቀቀው ሰነድ ላይ አስታውቋል። ይህ ውሳኔ፣ የማኅበረሰቡን ግንዛቤ እና ክሪፕቶ ከረሲን የሚያካትት ባለመኾኑ፣ «ለኅብረተሰቡ ደኅንነት የተወሰደ ርምጃ ነው፤» የሚለው ቃል ካሳ፣ ይኹን እንጂ ማኀበረሰቡም ኾነ የመንግሥት አካላት ስለ ጉዳዩ ማወቅና ከዘመኑ ጋራ ለመራመድ ዝግጁ መኾን ይጠበቅባቸዋል፤ ይላል። ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት፣ በገንዘብ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለሥልጣናት የእጅ ስልክ ላይ በመደወልና በጽሑፍ መልእክት ለቃለ መጠይቅ ያደረግነው ጥረት አልተሳካም። በተመሳሳይ፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኀይል አገልግሎት ድርጅት፣ ከቢትኮይን ገቢ የሚደረገው የውጭ ምንዛሬ(ዶላር) ፍሰት፣ ተገቢው የኀይል አቅርቦት መስመር ዝርጋታ ላይ ስለመዋሉ፣ እንዲሁም ሥራውን ለመሥራት ወደ ሀገር ለገቡ ተቋማት የማኅበረሰቡን የኀይል አቅርቦት ፍላጎት ባልተሻማ መልኩ ለማቅረብ እያደረጓቸው ስላሉ እንቅስቃሴዎች ጥያቄ ብናቀርብም፣ የኮምዩኒኬሽንስ ድሬክተር ሞገስ መኮንን፣ ከዚኽ ጉዳይ ጋራ በተያያዘ በቅርቡ ቀጣይ ሪፖርት እስኪወጣ ድረስ በጉዳዩ ላይ ቃለ መጠይቅ እንደማይሰጡ ገልጸውልናል። Read more